About

የልሳነ ግፉዓን አመጣጥ፣ ራዕይ፣ ዓላማዎችና ክንውኖች፣

የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጭ ግንባርና አጋሮቻቸው ታላቋንና ጥንታዊቷን ኢትዮጵያ ሃገራችንን የማፍረስና የህዝቧን አንድነትና አልበገር ባይነት የማዳከም፤ በአንፃሩ ደግሞ በኢትዮጵያ ፍርስራሽና በኢትዮጵያዊያን ኪሳራ ላይ “ታላቋን ትግራይ” የመገንባት አላማና ተልዕኮ አንግበው ከዘመቱብን ጊዜ ጀምሮ በዚህ ኋላቀርነት፣ድህነትና፣ ጦርነት ባጎሳቆለው ህዝብና በዚች በጠላቶቿ ጥርስ ውስጥ በገባች አገር ላይ በታሪካችን ተወዳዳሪ የማይገኝላቸው እጅግ ከፍተኛና ዘግናኝ ወንጀሎች ተፈጽመውብናል። እየተፈጸሙብንም የገኛል።

በተለይም ታላቁንና በአንድነቱ የአፍሪካ ኩራትና ተምሳሌት የሆነውን ኩሩውንና ጀግናውን የኢትዮጵያ ህዝብ በጎሳና በዘር ከፋፍሎ በማጋጨትና በማዳከም፤ በአንድነቷና በነፃነቷ ከ3ሺ ዘመን በላይ ፀንታ የኖረችን ታላቅና ሉዐላዊት ሀገር ዳር ድንበሯንና ታሪካዊ ቅጥሯን አፍርሶና ወደቦቿን ለተገንጣዮች አስረክቦ ከምን ግዜውም በላይ የተዳከመችና አቅመቢስ እንድትሆን በማድረግ፣ ታላቁን ህዝባችንና ወድ ሃገራችንን ለባዕዳን የበቀል ጥቃትና ዘረፋ አሳልፎ በመስጠት ታሪክና ትውልድ ይቅር የማይለው በደል እራሱን የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጭንኝ በሚለው ወራሪና ተስፋፊ ቡድን ፊታውራሪነት እየተፈፀመብን ይገኝል።

ይልቁንም ከህወሃት ምስረታ ጀምሮ እስከ አሁኗ ሰአት ድረስ ይህን ህወሃታዊ እኩይ ሴራና የሃገር መክዳት ወንጀል የተቃወሙ፣ በሃገርና በህዝብ ላይ እየተፈጸመ የሚገኘውን ፈረጀ ብዙ ጥፋት ለማስቆም በተንቀሳቀሱና፣ ለዓለም ህዝብ ባጋለጡ ወገኖቻችን ላይ እጅግ አሰቃቂና መጠነ ሰፊ የሆን የጀምላ እስራት፣ ግርፋት፣ ስደትና፣ ግድያ፤ … ወዘተ በመፈፀም ኢትዮጵያ ለኢትዮጵያውያን ማቆሚያ የሌለው የስቃይና የመከራ እስርቤት እንድትሆን የተደረገች ሲሆን፣ በአንፃሩ ደግሞ ሃገራችን ለህወሃት መሪዎች፣ አባላትና፣ ደጋፊዎቻቸው ተዝቆ የማያልቅ ሃብት ማካበቻ ገነት የሆነች ሲሆን፣ የታላቋን ትግራይ የመገንባቱ ተልዕኮ ኢትዮጵያንና ህዝቧን ከማተራመሱ ጎን ለጎን በስማችን በሚሰበሰበው ዓለምአቀፍ ብድርና እርዳታ እየተፋጠነ ይገኛል።

“ታላቋን ትግራይ” እንደ አንድ እራሷን የቻለች ነፃና ለዓላዊት ሃገር ከመገንባትና ከማስቀጠል አንፃር ቅድሚያ ተሰጥቶባቸው እየተከወኑ ከሚገኙት ዋና ዋና አላማና ተግባራት መካከል፡

1ኛ) የትግራይን ክልል የመሬት ይዞታ በማስፋት ከ1983 ዓ.ም በፊት ከነበራት ቅርፅና መጠን በአጅጉ የላቀች ማድረግ

2ኛ) ትግራይን ከጎረቤት ሃገራትና ከቀሪው ዓለም ጋር የሚያገናኛት የየብስና የባህር በር ባለቤት ማድረግ

3ኛ) ቀሪውን የኢትዮጵያ ግዛቶች በማፍረስ ለትግራይ ታላቅነትና ህልውና ስጋት በማትሆንና በተዳከመች ኢትዮጵያ ላይ       ታላቋንና በኢኮኖሚ፣ በቴክኖሎጂ፣ በትምህርት፣ በጤና፣ በወታደራዊ ሃይል፣ በኢንዱስትሪ፣ … ወዘተ የበለፀገችውን ትግራይ   መገንባት ሲሆኑ

4ኛ) ከላይ ለተዘረዘሩት ህውሃታዊ እቅዶችና “ታላቋን ትግራይ” ለመገንባት ለሚደረጉ ተመሳሳይ ድረጊቶች እንቅፋት ወይም           ስጋት የሆነን ሁሉ ያለምንም ርህራሄና ሃዘኔታ ማስወገድ ናቸው።

የትግራይ ሕዝብ ነፃ አውጭ ግንባር (ወያኔ) ከላይ በ1ኛ ተራ ቁጥር ላይ የተቀመጠውን አላማ ለማሳካት በሚያደርገው የእብደትና የእብሪት ጉዞ ጥንታዊ፤ ታሪካዊና፤ እጅግ ለም የሆኑትን የጎንደር (ወልቃይት፤ ጠገዴ፤ ጠለምት) እና የወሎ (ቆቦ፣ ራያ፣ አዘቦ) መሬቶችን ከ1972 ዓ.ም ጀምሮ በወረራ በመያዝ በይፋ ወደ ትግራይ ክልል ግዛት ውስጥ በማስገባት የትግራይ አካል በማደረግ የተከለሉ ሲሆን፤

በ2ኛ ተራ ቁጥር የተቀመጠውን ግብ ለማሳካትና ወደ ጎረቤት ሃገር ሱዳን መውጫ የሚሆን የየብስ ወደብ ለማግኘትና፤ ያለጥርጥር የታላቋ ትግራይ አካል አድርጎ ለማስቀመጥ ሲባል የጎንደር ታሪካዊ ለም መሬቶች በተለይም የወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ያለነዋሪው ህዝብ ፍላጎትና ፈቃድ የአዲሲቷ ትግራይ አካል እንዲሆኑ ተደርገዋል፤

ይሁን እንጂ ጀግናውና የኢትዮጵያን ታሪካዊ ዳር ድንበር ለጠላት ሳያስደፍር አስከብሮ የኖረው ህዝባችን የአባቶቹን ዕርስት የኢትዮጵያና የህዝቧ ጠላት ለሆነውና ለተስፋፊው የህወሃት ወራሪ ቡድን ማስረከብና ማንነቱን ተነጥቆ ያለአባቱ ትግሪያዊነት በሃይል ተጭኖበት መኖርን ባለመፍቀዱ ከላይ በ4ኛ ደረጃ ላይ ከተቀመጠው “ታላቋን ትግራይ” እውን የማድረግ አላማ አደናቃፊና በግንባር ቀደምት ጠላትነት እንዲፈረጅና፤

ቀደም ሲል በኢትዮጵያዊነቱ ብቻ በ3ኛ ተራ ቁጥር ከተቀመጠው ህወሃታዊ የጥፋት ኢላማ ማምለጥ ያልቻለው የወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ማህበረሰብ በሁሉም መስክ ለህወሃትና አጋሮቹ እኩይ ሴራ መሳካት እንቅፋት በመሆኑና በአንፃሩ ደግሞ ለታላቋ ኢትዮጵያ ሉዓላዊነት መጠበቅና ለህዝቧ አንድነትና ሰላም መረጋገጥ ዋስትና ሆኖ በመገኘቱ የህወሃት የዘር ፍጅት ኢላማ ወስጥ እንዲወድቅ የግድ ሆኗል።

ስለሆነም የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጭ ግንባርና አጋሮቻቸው የወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ማህበረሰብን በማጥፋት አካባቢውን በትግሪያዊነት ብቻ መተካት አማራጭ የሌለው መንገድ አድርገው በመውሰድ በወገኖቻችን ላይ ዓለም በአጅጉ የተፀየፈውንና ያወገዘውን “አንድን ዘር አጥፍቶ በሌላ ዘር የመተካት” (genocide) ወንጀል ከ1983 ዓ.ም ጀምሮ ህወሃት መራሹ ወራሪና ተስፋፊ ቡድን በኢትዮጵያ መንግስት ስም፣ ስልጣን፣ ሃብትና፣ የጦር ሃይል በመታገዝ የወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ዘርን አጥፍቶ በትግሪያዊነት በመተካት ላይ ይገኛል።

በዚህ የህወሃትና አጋሮቹ የወንጃል ሂደት ውስጥ፡

1ኛ) ብዙ ታሪክ ነጋሪ አዛውንቶች ከቤቶቻቸው ተለቅመው በመወሰድ ደብዛቸው እንዲጠፋ

2ኛ) በብዙ ሺ የሚቆጠሩ የዚህ አካባቢ ጀግኖች በየምክንያቱ እስከነሕይወታቸው በሠው ሰራሽ ጨለማ ጉድጓድ ውስጥ         በማሰር ሰውነታቸው ተልቶና ማሽሾ እንዲያልቁ ተደርጓል

3ኛ) ያለማውን የእርሻ መሬቱን በመንጠቅ ከ 600,000 በላይ የትግራይ ብቻ ተወላጆችን በቦታው አስፍረዋል

4ኛ) ባልረባቡ ምክንያቶች እጅግ ከፍተኛ ቅጣቶችን በሕዝቡ ላይ በመበየን ዓይን ያወጣ የንብረትና የገንዘብ ዘረፋዎችን አካሂደዋል

5ኛ) በብዙ ሺ የሚቆጠሩ የወልቃይት ጠገዴ ተወልጅ ኢትዮኦጵያውያን እህቶች ተገደው ከትግራይ ወንዶች እንዲወልዱ፤

6ኛ) መጠኑ እጅግ የበዛ ሕዝብ ቦታውን ለቆ እንዲሰደድ፤

7ኛ) በቀረው ወገን ላይም ነፃነት ተንፍገው በተወለዱበት መንደራቸው እንደሁለተኛ ዜጋ ሁነው እንዲኖሩ ሆኗል

8ኛ) የባህል፤ የቋንቋና፤ የህሊና ክፍተኛ ተጽእኖ እየተደረገበትም ነው፡ ወዘተ…

ታዲያ ምንም እንኳ የወልቃይትና ጠገዴ ችግር የሚፈታው የኢትዮጵያችን ችግር ሲፈታ ማለት የትግራይ ነጻ አውጭ ድርጅት ሲወገድ መሆኑን ብንገነዘብም ወያኔ በወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ተወላጅ ኢትዮጵያዊያን ላይ የፈፀመችውንና እየፈጸመችው ያለውን ከባድ ወንጀል እስከነማስረጃው ዘግቦ ለሚመለከታቸው የፍትህ ተቋማትና ተቆርቋሪ ድርጅቶች ማቅረብና መከታተል ሲሆን፣ ይህ ድርጊት እየተደረገ ላለው ኢትዮጵያዊ ትግል ያጎለብታል አስተዋጽኦም ይኖረዋል ብለን ስለምናምንም በውጭ ሀገር ያለን የወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ኃላፊነታችን ለመወጣት ያመቸን ዘንድ ልሳነ ግፉዓን ድርጅት (Voice of the Victims Org.)_በሚል ከ2009 (እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር) ጀምሮ በሰሜን አመሪካ በህጋዊ መንገድ ተደራጅተናል።

ራዕይ

የትግራይ ሕዝብ ነፃ አውጭ ግንባር በወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ኢትዮጵያዊ ወገን ላይ የፈፀመችውን እየፈጸመቸው ያለውን “አንድን ወገን አጥፍቶ በሌላ የመተካት ወንጀል (genocide & ethnic cleansing) አጋልጦ ወንጀለኛዋ ድርጅትም ሆነ ተጠያቂ ግለሰቦችን ወደ ፍርድ የሚቀርቡበትን መንገድ መሻት ሲሆን እንዲህ አይነቱ ኢ-ሰብአዊ ድርጊት በአገሪቱ እንዳይደገም በአንፃሩም በመላው ኢትዮጵያ ነፃነት ፍትሕ ሰላም ሰፍኖ ማየት ነው።

ተግባራት

  1.   ወያኔ በዚህ አካባቢ ለረጅም ዘመናት ለፈፀመቻቸው ወንጀሎች በቂ ማስረጃዎችን ማሰባሰብ
  2.  የተሰበሰቡ ተጨባጭ ማስረጃዎች ለሚመለከታቸው ኢትዮጵያዊም ሆነ ዓለምአቀፍ ተቋማት ማዳረስና ውጤት እንዲኖራቸው መከታተል፤
  3.  በማስረጃ የተደገፉ ወንጆሎች የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆነ የዓለምአቀፍ ኅብረተሰብ እንዲያውቃቸው ማድረግ፤ የተነጠቁ መሬቶችን ለባለመሬት፤ የተዘረፈው ንብረት ለባለንብረቱ የሚመለሱበትን መንገድ መሻት፤ የታሰሩ ወገኖችን እንዲፈቱ፤ በግፍ ለተገደሉት ቤተሠቦች ካሣ እንዲሰጡ ጥረት ማድረግ፤
  4.  የተሰበሰቡትን ተጨባጭ ማስረጃዎች ዘግቦ በማኅደር ማስቀመጥ፤
  5. በወያኔ ግፍና በደል የተፈፀመባቸው ግለሰቦችም ሆነ ቤተሰቦች መርዳት፤
  6. ለአካባቢውም ሆነ ለመላው ኢትዮጵያ ዘላቂ ፍትህ ነፃነት ሰላም ለማምጣት ለሚጥሩና ለሚታገሉ ኢትዮጵያዊ ድርጅቶች ድጋፍ መስጠት ወዘተ…

ዋና ዋና ክንዋኔዎች

  1. ልሳነ ግፏዓን የህጋዊ ሰውነት ከማግኘቱ በፊት በ2003 (እ አውሮፓውያን አቆጣጠር) ለኢትዮጵያ መንግስት ተብየው ለመቶ አለቃ ግርማ ወ/ጊዎርጊስ ቅጅ ለጠ/ሚ፣ ለፓርላማው፣ ለፍትህ ሚ.፣ ለውጭ ጉዳይ ሚ.፣ ለክልሎች ወዘተ.. የታሰሩት እንዲፈቱ፣ ሰፈራ በወልቃይት ጠገዴና ጠለምት እንዲቆም ፣ የተፈናቀሉት እንዲመለሱ፣ እነዚህ ግዛቶች ወደነበሩበት ጎንደር ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲመለሱ ወዘተ…
  2. በተደጋጋሚ ባገኘናቸው ውስን ሚዲያዎች ‘መልስ ያጣ የህዝብ እንባ’፣ ‘ሰሚ ያጣ የህዝብ ጩኸት’ ወዘተ በመሳሰሉት መጻጽፎች የኢትዮጵያ ህዝብ ጀሮ እንዲደርሱ ሞክረናል
  3. በወያኔ ታፍኖ የተያዘውን መረጃ እጅግ አዳጋች በሆነ መንገድ የብዙ የተገደሉና ታፍነው የጠፉ ወገኖቻችንን ስም ዝርዝር በማዘጋጀት በተለያዩ ሚድያዎች በማሰራጨት በሁኔታው ተጠቃሽ እንዲሆኑ ማድረግ
  4. ለተለያዩ የአለም አቀፍ መንግስታትንም ሆነ የመብት ጠባቂ ድርጅቶች ሁኔታውን ማሳወቅ
  5. የነዚህ አካባቢ ተወላጆች በስደት በሚደርስባቸው የስደተኛ መብትን የማስከበር በተመለከተ ለUNHCR, Amnesty International, Government of  The Sudan etc..የአቤቱታ ደብዳቤዎችን በመላክ
  6. ከ2012 ጀምሮ ልሳነ ግፉዓ በጥናት የተመሰረተ ስትራተጂ በመንደፍ የወልቃይትን ጉዳይ በሚመለከት በቅድሚያ ሚዲያዎችን በመጠቀም ከኢትዮጵያ ህዝብ ጀሮ ማድረስና ህዝቡ በተለይም ጎንደሬው፣ አማራውና ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ በሙሉ  ጉዳዩ የኔ ጉዳይ ነው ብሎ እንዲይዘው መጣር ነበር። በዚህም መሰረት ግቡን አሳክቷል። ምስጋናችን ለኢሳት ቴሌቪዥንና ራዲዮ፣SBS, Mahder, Hibr ወዘተ… እና የተለያዩ ድህረገጾች እናቀርባለን።
  7. ከተለያዩ የኢትዮጵያ ድርጅቶች ጋር መተባበር